Tuesday, March 19, 2019

ህዝቢ ትግራይ መን'ዩ?

ህዝቢ ትግራይ መን'ዩ? ምስ ፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክረስት ዝተገበረ ሓፂር ፃኒሒት (ብቛንቛ ኣምሓርኛ)፣ ሰናይ ንባብ።

ፕሮፌሰር፣እስኪ ጥያቄየን ታሪክ ምንድን ነው በሚለው ልጀምር፤

ፕሮፌሰር፦ በእውነት ለአክብሮታቹ ኦጅግ አድርጌ አመሰግናለው፤….ታሪክ ማለት ከብዙ ዘመናት በፊት እስከ አሁኗ ሰከንድ ድረስ የተከናወኑና እየተከናወኑ ያሉ የተለያዩ ስራዎችን ከእውነተኛ መረጃ በመነሳት ስለ አንድ ሀገር ህዝብና መንግስት፣የስራ የባህል፣ የቋንቋ፣ የወግና ስርዓት የመሳሰሉትን የምናጠናበትና የምንማርበት መሳርያ ነው፤በጠቅላላ ታሪክ እውነትን መፈለግ ማለት ነው።

ጠያቂ ፦ መልካም፤ አጠር ባለ መልኩ ዛሬ የምንነጋረው በኢትዮጲያ ህዝቦች ዙርያ ይሆናል፣ ከሰሜን ልጀመርና ትግሬዎች ማናቸው፤ ከየትስ መጡ፣ ምንስ ለዚች ሀገር አበረከቱ?


ፐሮፌሰር፦ እሺ…ምን መሰለህ በመጀመሪያ ለትግራይ ህዝብ ልዩ ምስጋና ማቅረብ እፈልጋለው፣ ኢትዮጲያን የታሪክ ማማ ላይ እንድትቀመጥ ያስቻለ እኮ ይሄ ታላቅ ህዝብ ነው፡፡ ከጥንቱ የኢትዮጲያን ግድግዳ ያቆመ፣ ጣራውን ያጸና፣ የራስዋ ትውፊት እና ባህል እንዲኖራት ያረገ፤ ሀገራችን የዘመናት ዑደት ስፍር ቀምራ፣ የራሷን ፊደል ቀርጻ፣ ቁጥር መቁጠሪያ አኀዝ ይዛ፣ በነጻነት ታፍራ እና ተከብራ እንድትኖር ያደላደለ ህዝብ፣ አስደናቂ ጠቢባን ነገስታት እና ተወዳዳሪ የሌላቸው እልፍ አእላፍ ጀግኖች ማፍለቂያ፣ በአፍሪካ ለመጀመሪያ ጊዜ ክርስትናን፣ ዘጠኙ ቅዱሳንን እና እስልምና ሀይማኖት በክብር ተቀብሎ በስነስርአት ያስተናገደና ያኖረ ህዝብ ነው። ስንቱን ልንገርህ የኩራታችን ምንጭ፣ መነሻን ነው ብልህ ምንም ክፋት አይኖረውም፡፡ ለዚህም ነው ልጄን በራስ አሉላ ስም የሰየምኩት። ልጄ አሉላ ፓንክረስት (Alula Pankhurst) ይባላል፡፡ ይሄ ህዝብ ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለው፡ ሀገሩን የሚወድ፣ እጅግ ሃይለኛ ጦርነት ገጥሞ የማያፈገፍግ ምርጥ ተዋጊ፣ ቸር ተባባሪ እና እንግዳ አክባሪ ነው። የትግራይ ሕዝብ ከዓድዋ ጦርነት በፊት የአውሮፓ ወራሪዎችን ድባቅ መትቶ ያባረረና ያሸነፈ ነው። ለምሳሌ ከአድዋ ጦርነት በፊት የትግራይ ሕዝብ ብቻውን ኢጣሊያን፡ ቱርክን ፡ ግብጽን ለሶስት ጊዜ ያህል፡ የግብጽ፡ የአሜሪካና የእንግሊዝ የተቀናጀ ጦርን፡... በጉራዕ፣ በጉንደት፣ በኩፊት፣ በሰሐጢ፡ በዶግዓሊ፣ በተድዓሊ፡ በምጽዋ ላይ አሸንፏል ይህም በተለያዩ የኢትዮጵያና የውጭ የታሪክ ሙሁራን ተጽፏል። ኘገር ግን አንዳንድ ሰዎች ሳያውቁ ወይም ሆን ብለው የነጭ ወራሪ ለመጀመሪያ ጊዜ የተሸነፈው በዓድዋ ላይ እንደሆነ ሲናገሩ ይደመጣል ይህ ግን ስህተት ነው። እንደሚታወቀው በዓድዋ ጦርነት ወቅት ከፍተኛውን ተጋድሎ የፈጸመው የትግራይ ሕዝብ ቢሆንም፧ የሌሎች ብሔረሰቦች ተሳትፎም ነበር። የትግራይ ሕዝብ በወቅቱ የጣሊያንን ጦር ጠንክሮ ባይመክተውና ባያስቆመው ኖሮ የኢትዮጵያ ሰራዊት ያን ሁሉ ኪሎ ሜትር በኋላ ቀር መጓጓዣ ተጉዞ ዓድዋ እስኪደርስ ድረስ ጣሊያን መላዋን ኢትዮጵያ ይቆጣጠራት ነበር።

ጠያቂ ፦ የመጀመርያ ትግሬዎች መኖረያቸው የት ነበር?

ፐሮፌሰር፦ ትግራውያን የኢትዮጵያያ ጥንተ ነዋሪዎች ከሚባሉት ውስጥ ግንባር ቀደሞቹ ናቸው። ዋናው ቁም ነገር ቀድሞ መኖርያቸው የት ነበር የሚለው ነው። እንግዲህ ታሪኩ እጅግ ረጅምና ውስብስብ ቢሆንም አጠር ባለ መልኩ የነበሩ ዋና ዋና ሁነቶችን ለመናገር እሞክራለው፡፡ እንደሚታወቀው እግዚአቢሔር ሰዎች በሰሩት ሀጥያት የተነሳ፣ ጻድቅ ከሆነው ኖህና ቤተሰቡ ውጪ ዓለምን ሁሉ በጥፋት ውሀ ደመሰሰ፡፡ እግዚአቤሔርም ለኖህና ቤተሰቡ ዳግመኛ ዓለምን በጥፋት ውሀ እንደማያጠፋት በሰማይ ላይ ቀስተ ደመናውን በማኖር ቃል ኪዳን ገባለት። በዚህም መሬት በኖህ ቤተሰቦች ማለትም በነገደ ሴም፣ በነገደ ያፌትና በነገደ ካም ከጥፋት ውሀ ጀምሮ መቶው አመት እስኪፈፀም ድረስ ያለ ልክ ቁጥራቸው በዛ። አዲሷ ምድርም እንደገና በሰው ተሞላች፡፡ ወላጆች ለልጆቻቸው ወደ መርከብ ከገቡት በቀር የጥፋት ውሀ መጥቶ ሰውንና እንስሳን ሁሉ እንዳጠፋ ይተርኩላቸው ስለ ነበር፧ በጥፋት ውሀ የሆነውን ሁሉ የሚያስታውሱ ወይም ወሬውን የሰሙ ሁሉ የሰው ክፋት ያንኑ የመሰለ ቅጣት እንደገና መልሶ ያመጣብናል እያሉ ይሰጉ ነበር፡፡ ሰዎች በሚሰሩት ሀጥያት የተነሳ እግዚአቢሔር አለምን በድጋሜ በጥፋት ውሀ ያጠፋታልና ከነዚህ ሰዎች መለየት አለብን በማለት እንዲሁም ኑ ለእኛ ራሱ ወደ ሰማይ የሚያደርስ ግንብን እንስራ፣ በምደርም ላይ ሳንበታተን ስማችንን እናስጠራ በማለት በ “ጢ(ት)ግሪስ” ና “ኤፍራጢስ” አካባቢ የሚኖሩ ህዝቦች ራሳቸውን ለመለየት ታላቅ ግንብ ለመስራት ተማከሩ፡፡ ከነዚህ ህዝቦች መካከል የትግራውያን ቀደምት ዘሮች ዋነኛ ተሳታፊና ባለቤት ነበሩ፡፡ የሰው ልጅ ታላቅ ስልጣኔና ጽሁፍ የተጀመረውም በነዚህ ወንዞች ኣካባቢ ነው፡፡ ትግራይ-ትግሮት- የሚለው ስምም የዚህ ህዝብ ቀድሞ መኖርያ ከሆነው ጢግሪስ (ቲግሪስ) –tigris-ከሚባለው የስልጣኔ ማእከል ከሆነው ባቢሎን ሞሶፖታሚያ አካባቢ ከሚገኘው ታላቅ ወንዝ ስም የተገኘ ነው ብለው የሚከራከሩ ብዙ የታሪክ ሰዎች አሉ፡፡ ስለ ስሙ በኋላ እመለስበታለው። በእንዲህ ትግራውያን እና ሌሎች አያሌ ነገዶች(ህዝቦች) በህብረት ታላቁን የባብል ሰናኦር ግንብ በኢፍራጠስ ወንዝ ዳርቻ በስተ ምዕራብ አቅጣጫ ሲገነቡ ቋንቋቸው በ2247 ቅ.ል.ክ ስለተደበላለቀ ወደ ተለያዩ የአለማችን ክፍሎች ተበታተኑ፡፡ ትግራውንም አንጸባራቂ የሆነውን ስለጣኔያቸውን እና የጽሁፍ ጥበባቸውን ይዘው በ2000 ዓመተ ዓለም አካባቢ በሰሜን(ላይኛው) ቀይ ባህር በኩል አርገው በመሻገር ወደ አፍሪካ ምድር በመግባት ወደ ግብጽ(ምስር) አመሩ። ከብዙ ዘመናት ጉዞና እልህ አስጨራሽ የማያባራ ጦርነት በኋላ በኃይል የግብጽን በትረ መንግስት በመዳፋቸው ስር በማስገባት፣ በአፍሪካ መሬት የመጀመሪያ መቀመጫቸውን በዚያ ምድር አደረጉ። ሀገሪቷንም ወረሷት። ለብዙ ምእተ አመታትም ግብጽን በብልሃት በጥበብና በማስተዋል መርተዋል። የሚገርመው ነገር ደግሞ ተቀዛቅዞ የነበረውን የፒራሚድ ስራ እንደገና ነፍስ የዘራበት ይሄ ህዝብ ነው። እነዚህ ፒራሚዶች ፍጹም የግንበኝነት ጥበብ እና ልዩ የሂሳብ ቀመር የሚሹ ናቸው። ትግራውያንም ለዚህ በጣም የሚመጥኑ ነበሩ። እንዴት ብትለኝ ከምስራቅ ይዘውት የመጡት ስልጣኔያቸውን እዛው ከቆያቸው ጥበብ ጋር በማጣመር ቀድሞ ከነበሩት አያሌ ፒራሚዶች የተሻሉ ፒራሚዶችን ማነጽ መቻላቸው ነው። ጠንካራ የአእምሮ እና የጉልበት ሰራተኞችም ናቸው። ብዙ የታሪክ መጻህፍትም “የግብጽን ፒራሚዶች የገነቧቸው ኢትዮጵያውን ናቸው ሲሉ ትግራውያንን እየገለጹ መሆኑን መዘንጋት የለብህም። ተጋሩ ፒራሚዶቹን የሰሩት ምትሃት መሰሎቹን አስደናቂ የአክሱም ሓወልቶች ከመትከላቸው ብዙ ሺ ዓመታት አስቀድሞ ነው፡፡

ጠያቂ፦ የተከበሩ ፕሮፌሰር እንዴት ትግራውያን አሁን ወደ አሉበት ቦታ ሊመጡ ቻሉ?

ፕሮፌሰር፦ ትግራዉያን እንደ ሌሎቹ ስርወ መንግስታት የራሳቸውን ፒራሚዶች በግብጽ ምድር ከሰሩ በሁዋላ ሃይላቸውና አንድነታቸው እየላላ መጥቶ በሌሎች ሃይሎች ተጽእኖና ስር ወደቁ በዚህም ግብጽን በመተው መሰደድ ግድ ሆነባቸው። እነሱም ከጠላቶቻቸዉ ጋራ አንገት ለአንገት እየተናነቁ ጥቂት ጎሳወች ወደ ምድረ እስራኤል አካባቢ፤ አብዛኞቹ ግን የግብጽን ደቡባዊ በረሃ በመሰንጠቅ አሁን ሰሜን ሱዳን፤ ቀይ ባህር ፤ ሰሜን ኢትዮጲያ እና ኤርትራ አካባቢ ተሰባስበው መኖር ጀመሩ፡፡.መለያየታቸው ያደረሰባቸውን መአትና ፍዳ በመረዳትም እንደገና ሃይላቸውን በማጠንከር ማንሰራራት ጀመሩ። ለንግድ እና ለተለያዩ ተግባራት በሚያመች መልኩ ወደ ባህሩ በመጠጋት የደአማት መንግሥታቸውን መሠረቱ። በመቀጠልም የአክሱም መንግስትን መሠረቱ። የግዛት ወሰናቸውም እጅግ ሰፊ የሆነ ሲሆን ከሰሜን ቀይ ባሕር እስከ በናዲር (የአሁኑ ሞቃዲሾ ) የእነሱ ግዛት እንደነበር የታወቀ ነው። ይሄ ብቻ ሳይሆን የዛን ጊዜ ኢትዮጲያ ድንበሯ በሰሜን እስከ ግብጽና ሊቢያ ፤ በምዕራብ እስከ ቻድና ምዕራባዊ አፍሪካ ፤ በደቡብ እስከ ዩጋነዳ ነጭ ኣባይ ፤ በምስራቅ እስከ ሰሜን የመን ፤ ሲናሞሞፎሩስ ህንድ ውቅያኖስ መዳረሻ ድረስ የተለጠጠ ነበር፡፡ የተጋሩ ጎሳዎች እርስ በእርሳቸው እየተባበሩ አንድ እንድ ጊዜም እየተለያዩ ብቻ ለብቻ እስከ አምስት የሚደርሱ ንገስታት ነበሯቸው። ነገስታቱም መዲናቸውን አሁን ሱዳን ውስጥ በሚገኘው መርዌ እና ትግራይ ውስጥ በምትገኘው አክሱም እየተመላለሱ ሰፊውን ግዛት ያስተዳድሩ ነበር። የታሪክ መጻህፈት እንዲህ ይላሉ ፦ አክሱምንም ከሠሩ በኋላ መርዌንም ሠሩ።…..ያን ሰፊ ግዛት በጥሩ ሁኔታ ለማስተዳደር ሲሉ አንዱ አክሱም ላይ አንዱ መርዌ ሱዳን ላይ ነገሡ። ይህም በ1000 ዓም ቅድመ ልደተ ክርስቶስ ነበር ። ስለ ታሪኩ ካወሳን ዘንድ፥ ይሄ ዛሬ ሱዳን የተባለው ምድር ሁሉ በዓረቦች ወረራ ስር ከመውደቁ በፊት ቢያንስ ለ2500 ዓመታት ያህል የተጋሩ ግዛት ነበር። ጥንት የሚታወቀው ኑብያ ተብሎ ነበር። መናገሻውም መርዌ ነበር። የዛሬ 2900 ዓመት ግን ሱዳን ይባል ጀመር። ይህ ስም የወረደው ከአፄ አክሱማይት እናት ከንግሥት ሳዶንያ ነው። እሱ በህፃንነቱ የግብጽ ፈርኦን ሆኖ እስከሚያድግ ድረስ እስዋ በትግራውያን ሰራዊት ጠብቆት ስር ሆና ዙፋኑን እየጠበቀች በሱ ስም ቻድን ፣ግብፅን፣ ሊብያን እና የዛሬውን ሱዳን ታስተዳድር ነበር። በዚህ ምክንያት፥ ከሳሃራ በርሀ በታች ያለው ምድር በሙላ ሳዶንያ ተባለ። ቀስ በቀስ ተለውጦ ሱዳን ሆነ። እንዲያውም ኑብያ ውስጥ የነበረው መርዌ ለዛ አካባቢ እንደ ዋና መናገሻ ከተማ ሆኖ ያገለግል ነበር። ቢያንስ 14 የኢትዮጵያዊ ትግራውያን ሴቶች ህንደኬ በሚል ማእረግ በንግሥትነት በተከታታይ ዛሬ ሱዳን ፤ ግብፅና ፤ ሊብያ የሚባሉትን ሃገሮች ለ1000 ዓመት ያህል ገዝተዋል። ትግራውያንም በዚ ዘመን ብዙ አስገራሚ ተጋድሎዎችን አድርገዋል። ፋርሶችን ደመስሰዋል ፤ ግሪኮችንም ድባቅ መትተው ስለ አስደናቂ ተጋደሏቸው ‹‹tigri-ትግሪ›› ነብሮች ተብለው በታላቁ እስክንድር ተሰይመዋል። ትግራዋይ ለሚለው ስምም መነሻው ይህ ነው፡፡

ጠያቂ፦ ትግሬ ስለሚለው ስም እዚህ ጋር ላቁሞትና እስኪ ብዙ ሰዎች አክሱም የሚለው ቃል ትርጉሙን አያቁትምና ምን ማለት እንደ ሆነ ይነግሩናል?

ፕሮፌሰር፦ ጥሩ ጥያቄ ነው። አክሱም የሃገራችን ስልጣኔ ጫፍ ማሳያ ናት። አንዳንድ ጸኃፊያን አክሱም የሚለው መጠርያ ከአፄ አክሱማይት የመጣ ነው የሚሉ አሉ። የቅርብ ሳይንሳዊ ጥናቶች እንደሚያሳዩን ግን ታሪኩ ወዲህ ነው። አክሱም የነገስታት የበአላትና የብሄራዊ ስርአቶች መከወኛ መንበር እንደ መሆኗ መጠን ዘላለም “የንግስናና የድግስ ስርዓቶች” የሚፈጸሙባት መንደር ነበረች … የ”ኩስሚ” መንደር! “ኩስሚ” ማለት በትግርኛ “ድግስ… ግብዣ… ታላቅ ግብር” ማለት ነው! ስለዚህ “አኩስም”(አክሱም) ማለት ስርወ-ቃሉ “ኩስሚ” የሚለው ሲሆን “አኩስም(አክሱም) ማለት ደግሞ “ደግስ…ግብዣ አድርግ…ግብር አብላ” ማለት ነው።
ለምሳሌ :-“መብል” ብሎ “አብላ”
“ትምህርት” ብሎ “አስተምር” ሲል
“ኩስሚ” ብሎ “አኩስም” ይላል ማለት ነው!-ስለዚህ “አኩስም”(አክሱም) የቃላት ቅንብር ሳይሆን ከግዕዝ-ትግርኛ ማህጸን ቀጥ ብሎ ወጥቶ ከአንዲት ቃል የተፈጠረ ስያሜ ነው። የአክሱም መሪዎችም ነጋሲ ንጉስ በሚል ይጠሩ ነበር፡፡ ንጉሱቹ በዚህ ስም መጠራት የጀመሩት ክርስቶስ ሊወለድ 500 ዓመት ሲቀረው ነው። የትግራይ ስርወ መንግሰት አክሱም ላይ ለብዙ ግዜ መናገሻ ከተማውን አጽንቶ መኖሩ ግልጽ ነው። እክሱምም ለብዙ ግዜ ገናና ህዝብ ሆኖ ቆይቷል::

ጠያቂ፦ ትግሬ የሚለው ቃልስ ከየት መጣ?

ፕሮፌሰር፦ ስም በቁሙ ከግብር የሚወጣ ቦታነትና አካልነት ህላዌና ህይወት ያለው ማናቸውም ሁሉ በየክፍሉና በየአካሉ በየራስ ቅሉ፣ በየዓይነቱና በየመልኩ በየነገዱ፤ በየዘሩና በየዘመዱ ተለይቶ የሚጠራበት የሚታወቅበት ነው፡፡ የትግራይ ህዝብ ከቀድሞ ዘመን ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ የተጠራባቸው በዙ ስሞች አሉት።
እነዚህም፦ ‹‹ሒክሶስ፤ ደብዓ፤ ሐመድ፤ አግዓዚ፣ ሳባ፣ ሐበሻ፤ በደው፣ ነጋዴ፣ ትግሬ›› የሚሉ ቃላት የጥንት ትግራውያን የግል መጠሪያ ስሞች ናቸው። ከነዘህም መካከል አንዱ አግዓዚ ሲሆን ትርጉሙም መገዛት የማይወድ ነጻ የሆነ ህዝብ ማለት ነው፡፡ በጥንት ጊዜ የህንድ ንጉስ ራማ ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ ንጉስ ጲኦሪን ወግቶ አሸንፎ መንግስቱን በመቀማት ህዝቡን በጭቆና ይገዛ ጀመር፡፡ በዚህን ጊዜ የንጉስ ራማን(ብራህማ)ን ግፍ ያዩት ትግራውያን ሃይላቸውን በማሰባሰብ ራማን በመውጋት ራሳቸውንና ብዙ ሌሎች ነገዶችን ነጻ አውጥተው እንደገና ኢትዮጲያን በአዲስ መልክ መምራት ጀመሩ፡፡ በዚህም የተነሳ አግአዚያን ተባሉ፡፡ አግአዚ ማለት በግዕዝ አግዓዘ ማለት ሲሆን ትርጉሙም ነፃ አወጣ ማለት ነው። አግአዚያን ማለት ደግሞ ነፃ የሚያወጡ፣ መገዛት የማይወዱ አርበኞች ማለት ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ በብዙ ህብረተሰብ ዘንድ የሚታወቀው ትግሬ ወደ ሚለው መጠርያ ስም ስመጣልህ ደግሞ ቅድም እንደነገርኩህ ትግራይ-ትግሮት-ትግራዎት የሚለው ስም የዚህ ህዝብ ቀድሞ መኖርያ ከሆነው ጢግሪስ (ቲግሪስ) –tigris-ከሚባለው የስልጣኔ ማእከል ከሆነው ባቢሎን ሞሶፖታሚያ አካባቢ ከሚገኘው ታላቅ ወንዝ የተገኘ ስም ነው ብለው የሚከራከሩ ብዙ የታሪክ ሰዎች አሉ፡፡ ሌላኛው ትንታኔ ደግሞ ትግሬ ከበርቴ ነጋዴ ማለት ነው የሚሉ ኣንዳንድ የአረብ ጽሁፎች አሉ። ለዚህ መነሻ ምክንያቱ ጥንታዊያን ትግሬዎች ዝሆን እየጋለቡ፤ ግመልና ፈረስ እየጫኑ፤ ውቅያኖሱን ልዩና ምትሃታውያን በሚመስሉ ባለክንፍ መርከቦቻቸው አየሰነጠቁ የሚገበያዩ፤ በባህር እና በየበስ የተወጣላቸው ነጋዴዎች ስለነበሩ ነው። ነገር ግን በሃገራችን ባሉ የግዕዝ ድርሳናት ላይ ትግሬ የሚለው ግስ ስርወ ቃሉ እና አመጣጥ ታሪኩ ግልጽ በሆነ መልኩ ተሰንዶ ተቀምጧል፡፡ ታሪኩም‹‹እስክንድር በጥንት ዘመን የአክሱም ባሕረ ነጋሽን ሕዝቦች ሊያስገበር በዘመተበት ወቅት፣ ለጀግንነታቸውና ለኣስደናቂ ተጋድሏቸው ኣግዓዝያንን ‹ትግሪስ› እንዳላቸው ያስረዳናል፡፡ በንግስት ኒኮላህ ህንደኬ 3ኛ ጊዜ እንዴት በታላቁ የዓለም ንጉስ ትግሬ ተብለው እነደተሰየሙ ስታይ በጣም የሚገርም ታሪክ ነው፡፡ የአማልክት ግማሽ ልጅ የሚባለው ሄርኩለስ እንኳን ሊደፍረው አይችልም የተበላውን የግሪክና የመቄዶንያ ንጉስ የነበረውን ታላቁ እስክንድር፤ የአጋዝያንን መብረቃዊ ጥቃት ፍጹም ሊቋቋመው አልቻለም ነበር። በውጊያው የሽንፈት ጽዋውን ሲጎነጭም እንዲህ አለ፦ “አፍቶ ሰኢነ ትግሪ-ተጋሩ ..!” (ከነዚህ ተወርዋሪ የ”ነብር -ነብሮች” ጋር መዋጋት ከባድ ነው!) “ትግሪ(tigri)=ነብር ; …(በግሪክ) “ተጋሩ=ነብሮች); …(በግሪክ) …..ከዚያ ጊዜ ጀምሮ “አግአዚያን” የነበረው ስማቸው ቀስ በቀስ እየተረሳ ሄዶ “ትግራውያን” የሚለው ስም ደግሞ ይበልጥ እየገነነ ሄደ….! ይሄ ሁሉ የሆነውም በ5160 ዓ.ዓ፣ ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በ340 ዓመት(332 BCE) ወይም የዛሬ 2248 ዓመት ገደማ ነበር። እንግዲህ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ነው ትግራውያን የሚለው ስም በይፋ መጠቀም የተጀመረው። ትግሬ የሚለው ሰም ከ100 ዓመት በፊት የመጣ ሳይሆን ከጥንቱ ከጥዋቱ ጀምሮ የነበረ ነው። ምሳሌ ይሆንሀ ዘንድ መረጃ ላቅርብልህ ፣ ከ650 ዓመት በፊት ለሶሎሞናዊው ንጉስ ዓምደ ፅየን በተሰባበረ የአማርኛና ግእዝ ግጥም ላይ ትግሬ የሚለው ስም በደማቁ ተጽፎ ይገኛል፡፡ እንዲህም ይላል
‹‹ሓርበኛ ዓምደጽየን መላላሽ የወሰን፣
ወኸ እንደ መሰን መላላሽ የወሰን፤
ከገንዝ ጠጣን ምን ቀረህ በመሰን፣
ከባሌ አሊን ከደውሮ ኄደራን፣
ከአገው አቤት አዠርን፣
ከትግሬ ነገደ ክርስቶስ ይውረድ፤
ከጎጃም ጃን ክምርን ከጋፋት አወላሞን፣
በዳሞት ሞት ለሚን ማን ቀረህ በወሰን፤
ሓርበኛ አምደ ጽዮን መላላሽ የወሰን፡፡››
፤፤፤፤፤ልጨምርልሀ ከ560 ዓመት በፊት ለንጉስ ዘርአያቆብ በቀረበ መወድስ ትግሬ የሚለው ስም እንደገና ታገኘዋለህ፤ እንዲህም ይላል
‹‹….የለመደው በግዳይ፤
ዣን ዘርዓያእቆብ በድል ጸሀይ፣
ቀለበው እንደ እንቧይ፤፤
አፈረጸው እንደሎሚ አላዋልቶ ዋጋ ይታይ፣
በትግሬ በነገደ ዘእየወሰ ጋይ፣
ግብጽ የመጻ ፈርዘነይ የከመሩት ድንጋይ፣
ሰማ ዘርአያቆብ እንደይቤይ……፡፡
፠፠፠፠፠፠፠ ፠፠፠፠፠ ፠፠፠፠፠

No comments:

Post a Comment

Quick Guide to Every Herb and Spice in the Kitchen – በማድቤት ውስጥ የእያንንዱ ቅጠል እና ቅመም ፈጣን መመርያ

ደረቅ ቅጠሎች እና ቅመሞች አሳፎቲዳ (አሳፌቲዳ) – አሳፎቲዳ በህንድ አመጋገብ ውስጥ የምግብ መፈጨትን ለመርዳት የሚጠቅም ሲሆን የበሰለ ዝንጅብል ሽንኩርት ቃና ያለው ጠንካራ ሽታ አለው፡፡ አቾቴ ማጣበቂያ እና ዱቄት ...